በእንተ ርእስየ

Thursday, October 11, 2018

ሆድ አደሮች በቤተክርስቲያን


እግዚአብሔር ሰውን ሲፈጥር ሁለት ጠባይ እንዲኖረው አድርጎ ነው ይህም እንሰሳዊ እና መልአካዊ፡፡ እንደ እንሰሳ ይበላል፣ ይጠጣል፣ ይተኛል፣ ይሞታል ወዘተ፡፡ እንደ መልአክ ደግሞ ሕያው ነው፣ ያመሰግናል፣ ይነቃል፣ ባአጠቃላይ የነፍስን ፈቃድ እየተከተለ እግዚአብሔርን እንዴት እንደሚያስደስት ያስባል ያደርጋልም፡፡ ነገር ግን የሰው ልጅ አብዛኛውን ጊዜ ስለ ስጋው ሲያስብ ይኖራል፣ ማለትም ስለ ሆዱ ማለት ነው፡፡ በዓለም ላይ ብዙዎቻችን የምንዳክረው ስለ ሆዳችን ነው፡፡ ነገር ግን ከክርስቶስ ልበልጥብን አይገባም ምክንያቱም የዕለት ምግብ የሚሰጥ ራሱ አምላካችን ነውና፡፡
ባሁኑ ጊዜ ግን በስመ ክርስቶስ ወይም በስመ ማኅበር ለገዛ ሆዳቸው የሚሮጡ፣ የሚኖሩ፣የሚማሩ፣ የሚያገለግሉ፣ አንድ ክርስቲያን ያደርጋል ተብሎ የሚታሰበውን በሙሉ የሚያደርጉ እየመሰሉ ለገዛ ሆዳቸው የሚመላለሱ እየጨመሩ መጥተዋል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ለጊዜው የተናገረው ስለ ሐሰተኞች ነቢያት ማለት ስለ መናፍቃን ነበር ምክንያቱም ጌታችን በስሜ ይመጣሉ እንዳለው ሁሉ ዓላማቸው ስለ ክርስቶስ ሳይሆን ለገዛ ሆዳቸው ነው እንጂ መስቀል ላይ የተከፈለውን የክርስቶስን ዋጋ የሚሰብኩ አይደለም፤ ዓላማቸው ሆዳቸውን መሙላት ነው፡፡ ይህ እንግዲህ ራሳቸውን ለለዩ ለመናፍቃን ነው፡፡ እኔ መጻፍ የፈለኩት ግን ከውስጥ ሆነው ለክርስቶስ ወንጌል ጠላት የሆነውን፣ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት እየጣሰ ያለውን የውስጥ ሆድ አደርን ነው፡፡ ሆድ አደር! ስለ ክርስቶስ የሚሰብክ ይመስላል ነገር ግን ዓላማቸው ገንዘብ ማግኘት ነው፡፡ ገና ስጀመር የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት የተማሩትም ለገንዘብ፣ ወይም በልማድ ይሆናል፡፡ በእንዲህ ዓይነት የተማረ ሰው ነው የክርስቶስን ወንጌል ለዓለም የሚያዳርሰው! በፍጹም አይታሰብም እንዲህ ዓይነት ሰው ወንጌሉ ወይም የሐዋርያዊ ስራ በሚፈልገው ልክ ሳይሆን በራሱ ልክ ነው የሚያስበው፣ የሚያደርገው፣ የሚናገረውም፡፡ ሕዝቡ ባለው ሳይሆን እሱ ባለው ይራመዳል፣ በሕዝቡ ማንነት ሳይሆን በራሱ ማንነት ይለካል፡፡ አውደ ምህረት ላይ ለመውጣት ሕዝቡን ማወቅ ጉዳዩ አይደለም ሰሙ አልሰሙ፣ ተረዱ አልተረዱ ጉዳዩ አይደለም፡፡ የሕዝቡን ባህል፣ ቋንቋ፣ መልክእምድር፣ ዳራ ማወቅ አይፈልግም ግን የቤተክርስቲያናችን ሐዋርያዊ ስራ እንዲህ አይልም፤ ሕዝቡን ሳያውቁ ማስተማር የለማ፡፡
የክርስቶስ ወንጌል ሕዝቡ በሚሰማ ቋንቋ፣ በሚረዳው ባህል፣ ሕዝቡ ባለው የሃይማኖት ዳራ፣ የእውቀት ደረጃ፣ ሥነ ልቡና እና ወዘተ መሰረት ያደረገው መሆን ነበረበት፡፡ ጌታችን ባረገ በአስረኛው ቀን መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት በሰደደ ጊዜ የክርስቶስን ወንጌል ለዓለም ለማዳረስ መንፈሳዊ መሳሪያ ይሆናቸው ዘንድ 72 ቋንቋ ገለጠላቸው፡፡ በሐዋርያት ስራ ታሪክ የሕዝብን ቋንቋ ባለማወቅ ያጋጠማቸው ችግር ሰምተን አናውቅም ምክንያቱም ሆድ አዳሮች አልነበሩም፣ የክርስቶስን ወንጌል ለፍጥረት ሁሉ ለማዳረስ ነበር ዓላማቸው፡፡ ይህንን በታላቅ ትጋት ፈጸሙ ግን ሆድ አደሮች የሕዝብን ነገር ማወቅ ዓላማቸውም አይደለም፡፡ ሕዝቡን ሳያውቁ ለወንጌል ይሰማራሉ፤ ቋንቋውን ሳያውቁ እናስተምርህ ይሉታል የሕዝቡን ትቶ በራሱ ቋንቋ ያስተምራል ግን ሕዝቡ አይሰማም፡፡ ምን ያድርግ ሆዱ አልጎደለ፣ ደሞዙ አልተቋረጠ፤ ሊቋረጥ እንደሚችል እንኳን አለማሰቡ ገርሞኛል፡፡ ግን ሕዝቡ ከሃይማኖቱ እየኮበለለ ነው በሆድ አደሮች፡፡በተለይ በኦሮሚያ፣ በደቡብ፣ በጠረፋማው የሀገሪቱ ክፍል፡፡ ሆድ አደሮች ቤተክርስቲያን ውስጥ ለተስፋፋው ኃይለኛ ሙስና፣ዘረኝነት፣ተሀድሶ ና ሌሎች ግግሮች ምክንያቶች ናቸው ብዬ አምናለሁ፡፡ ልማት እየተባለ የሚወራውም ለሙስና መደበቅያ እንጂ መንፈሳዊ ሊማት አይደለም፤ ምክንያቱም በቤተክርስቲያን ሊማት ማለት ሕዝብን በወንጌል ማለምለም ነው፡፡
የሆድ አደራች ሌላው መገለጫው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለ ሀሳባቸው ምድራዊ ነው፡፡ የተሰጣቸው ፀጋ፣ ኃላፊነት፣ ክብር ሰማያዊ ቢሆንም የነሱ የዘወትር ጭንቀት ምድራዊ ነው፡፡ በስመ ወንጌል ወደማያውቁት ሕዝብ ከሄዱ በኋላ ያንን ሕዝብ የሚያደክሙበትን፣ የሚበትኑበትን፣ ከሞላላቸውም ማጥፋት የዘወትር ተግባራቸው ነው፡፡ ተተኪ ማፍራት ካለው ህብረተሰብ መሆኑ ቀርቶ በምድራዊ አጠራር ከዘራቸው ብቻ ያፈራሉ ሌላው በመካከላቸው እንዲገባ አይፈልጉም አይ መሸወድ ዋስትና የሌለው ሕይወት፣ ቤተክርስቲያንን የሚሰረስር የውስጥ ወንበዴ፣ ያልተነቃበት የውስጥ መናፍቅ፣ የመስቀል እና የወንጌል ጠላት፡፡ የአከባቢው ሕዝብ አገልግሎት ሲጠይቃቸው ዘረኞች ሆነው ዘረኞች እያሉ የሚደስኩሩ፡፡ ይህ እቅዳቸው በአካባቢው ያለው ሕዝብ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ባዳ እንዲሆን እና ሙሉ በሙሉ ትቶላቸው ሃይማኖቱን እንዲክድ ማድረግ ነው፤ እያደረጉም ነው በተለይ በኦሮሚያ፣ በደቡብ ክልሎች በመረጃ የተደገፈ ነው፡፡ የሆድ አደሮች ዓላማ ወንጌልን ማስፋፋት ሳይሆን ሆዳቸውን መሙላት፣ ባህላቸውን ማንጸባረቅ፣ ቋንቋቸውን ማሳደግ፡፡ ሃያ ዓመት ከሕዝቡ ጋር ኑረው የሕዝቡን ቋንቋ በመጥላት መልመድ እየቻሉ ወንጌልን ሳያስተምረው በአውደ ምህረት እየለፈለፉ ማንም ሳይሰማቸው ስንቱ ትቶላቸው ሄደ? ሆዳቸውን እየሞሉ ለክርስቶስ ወንጌል ጠላት የሆኑ ቤት ይቁጠራቸው፡፡ ነገር ግን ብያውቁ ኖሮ እና ትክክለኛ ሐዋርያ ቢሆኑ ኖሮ የሕዝቡን ቋንቋ ባወቁ ወይም ለማወቅ ጥረት ባደረጉ ነበር፡፡እዚህ አንድ አርቀው አሳቢ አባት የተናገሩትን ልንገራችሁ ‹‹ከምያሳዝነኝ ውስጥ ይህን ያህል በዚህ ክልል ኖሬ የክልሉን ቋንቋ አለመቻሌ ነው፤ መማር ያለብኝን የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ተምሬያለው ግን ማስተማር አልቻልኩም ምክንያቱም ሕዝቡ እንደማይሰማ እየተነገረኝ ነው፤ ደግሞ ምድራዊ መንግሥት እንኳን ከእኛ ተሽሎ የሚያስፈልጋቸውን ስጋዊ አገልግሎት እነሱ በሚሰሙት ቋንቋ እየሰጣቸው ይገኛል፡፡›› አሉኝ ግን እሷቸው ቁጭታቸውን እና እውነታውን ነው የሚናገሩት፡፡ እውነትም  ቀዳሚዋን ቤተክርሰቲያን ከምድራዊ አሰራር ወደ ኋላ ያስቀሩ ሆድ አደሮች አይመስላችሁም?
የሆድ አደሮች መጨረሻ ምንፍቅና፣ ጥንቆላ፣ ተሀድሶ መናፍቅነት በመጨረሻም ሰይጣን አምላኪዎች መሆን ነው፡፡ ስጀመር ዘረኝነት የሰይጣን መንፈስ ነው፡፡ የእውቀታቸው መለኪያ በሸመደዱዱት ልክ እንጂ ባመኑት ልክ አይደለም፤ ያውቃሉ ግን አይምኑም፡፡ ከዚህ የተነሳ የቤተክርስቲናችን የክህነት መስፈርት በሸመደደው ልክ እንጂ ባመነ፣ በተመሰከረለት መሆኑ ቀርቷል፡፡ ዛሬ ለተበላሸው የቤተክርስቲያናችን ሥርዓት ምንጩ ማን መሰላችሁ? ሆድ አደሮች አይደሉምን? የተማሩት ትምህርት የክርስቶስን ወንጌል ለማስፋፋት ሳይሆን ለሆዳቸው ስለሆነ በጎደለባቸው ጊዜ ከውጭ መናፍቅ ጋር እየታጃለሱ ሥርዓቷን ማበላሸት፣ ዶግማዋን መለወጥ ወዘተ፣ ስለ ገንዘብ ደግሞ የቤተክርስቲያንን ቅርስ መሸጥ፣ አብዛኛው በውጭ ሀገር ያለው በሺዎች የሚቆጠር የብራና መጻሕፍት መቼም በሆድ አደሮች ካልሆነ በስተቀር በሀገሬው ሕዝብ ነው የተሸጠው እንዳትሉ፡፡
የቤተክርስቲያን ሀብት ምእመናን ናቸው፣ የገቢ ምንጯም ከእነሱ ውጭ ማንም የላትም እንደ መናፍቃን ከውጭ የሚገባላት የላትም ነገር ግን ለዘመናት ገንዘብ በማጣት ወንጌል ከማስተማር ቦዝና አታውቅም ነበር፡፡ ሐዋርያቶቿ ይህ አይበግራቸውም ነበር ነገር ግን ዛሬ በሆድ አደሮች ሐዋርያዊ ስራዋ የታገተ ይመስለኛል ይህም የሆነበት ምክንያት ሕዝብን ያማከለ ሐዋርያዊ ስራ አልተካሄደም፡፡ ሰባኪ ከአድስ አበባ ማምጣት እንጂ ሕዝብ ማነው ይምለው ጥያቄ አይጠየቅም፤ ሰባኪውም ጠሪዎቹ በነገሩት ልክ ጮኾ ይሄዳል ለውጥ ግን የለም፡፡ በተለይ ኦሮሚያ ክልል ብዙ የሕዝብ ጉባኤ ይካሄድባታል ነገር ግን ለውጥ የለም ሕዝቡ አሁንም እየጠፋ ነው፡፡ በሕዝቡ ቋንቋ ይሰጥ ሲባል ዘረኞች፣ ተሀድሶ፣ፖለቲከኝ... ወዘተ ይባላል፡፡ ለመሆኑ ዘረኛው የትኛው ነው? በሕዝቡ ቋንቋ የማታስተምር ከሆነ ዝም ብለህ እንደምትጮኽ እንዴት አይገባህም? ሆድህ ካልጎደለ አይታወቅህም አንድ ቀን እንደምጎድልህ ማወቅ ግን ነበረብህ፡፡ ይህን የሚያደርገው እኔ አይደለሁም የሐዋርያት ጌታ በሃምሰኛው ቀን የወረደ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ብልጥ እና ሐዋርያ ብትሆን ግን በሕዝቡ ቋንቋ፣ ባህል መሠረት ባስተማርክ ነበር፡፡ ዘረኛ ሆነህ ነው እንጂ ይህን ዓመት ሁሉ በሕዝብ መሀል ኖረህ ቋንቋቻውን በለምድክ ነበር፣ ባህሉን በተረዳህ ነበር አንተ ግን የመጣህበትን ቋንቋ እና ባህል ስታራግብ ኖርክ ቤተክርስቲያንን ስለማትወክል አይደንቀኝም፡፡ ግን ቅድስት ቤተክተርስቲያንን ከመናፍቃን ይበልጥ በአንተ ስለተጎዳች ዝም አልልም፡፡ ምክንያቱም የቤተክርስቲያን ጠላት አምራች አንተ ራስህ ስለሆንክ ማለት ነው፡፡
የሆድ አደሮች መገለጫው ሌላው ወንጌል ባለማስተማራቸው የሕዝብ ቁጥር እየቀነሰ ሲሄድ የሚገባው ገንዘብ እንዳይጎድልባቸው በስመ ገቢ ማመንጫ እና በስመ ልማት ሕንጻ መገንባት፣ ማስገንባት ነው፡፡ ታቦተ ሕጉ ቆሞ ወንጌል ከማስተማር የገንዘብ ልመና መርሐግብር መብዛቱ፣ ገንዘብ ለማግኘት ተብሎ ጽላቱ የሚከብርበትን ቀን እስከመቀየር መድረስ፤ ለምሳሌ መስከረም 17 የመስቀል በዓል ስለሚከበር በዕለቱ ደግሞ ጉራጌዎች ወደ ተወለዱበት ስለሚንቀሳቀሱ ከእነሱ የሚገኘው ገንዘብ እንዳይቀር ተብሎ በዚህን ቀን የሚታሰበው የቀዳሜ ሰማዕት ቅዱስ እስጢፋኖስ በዓል ወደ ጥር 17 መሸጋገሩ ከውስጤ አልወጣ ያለ ክስተት ነው፡፡ ሌላው ደግሞ በአንድ አስተዳደር ስር ያሉ ተመሳሳይ መታሰቢያ ያላቸው አብያተ ክርስቲያናት ሁለቱም አንድ ጊዜ የሚነግሱ ከሆነ የሚገኘው ገንዘብ ስለሚጎድል የአንዱ ቤተክርስቲያን ጽላት እንዳይወጣ ተደርጎ የአንዱ ብቻ ሲወጣ ማየቴም አሳዝኖኛል፤ ለዚህ ነው ይህንን ጽሑፍ ለማውጣት የተገደድኩት፡፡ ባሁኑ ጊዜማ ሰለቸኝ ለስብከተ ወንጌል ማለትም የሥላሴ ሕንጻን ከማነጽ ይልቅ ድንጋይ ለመከመር የሚለመነው ገንዘብ፣ የሚሠራው ስራ ልዩ ነው፡፡ ይህ ጥቅሙ በምድራዊ መንግሥት ዘንድ ለመወደድ እንጂ በሰማያዊው ንጉስ ዘንድ እንደማያስከብር ይታወቃል፡፡ ሕዝቡ ኮብልሎ ስለሄደ፣ ወይም ስላልተማረ ምን አገባኝ በማለት ዝም ስላለ የሚጠይቃቸው የለም በራሱ አከባቢ በስመ ቤተክርስቲያንን የፈለጉትን ይሆናሉ፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ቤተክርስቲያንን ከዓላማዋ እና ከባሕርይዋ ውጭ ስለሚያደርጋት ብያስቡበት መልካም ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ለሕዝብ ናት እንጂ ለተወሰኑ ሰዎች የስጋዊ የገቢ ምንጭ እንድትሆን አይደለም፡፡
ሆድ አደሮች የሚኖሩት ሆዳቸው ይሙላላቸው እንጂ ስለ ቤተክርስቲያን ሥርዓት አይጨንቃቸውም፡፡ በቅዳሴ ሰዓት የሙዳይ ምጽዋት ፍተሻ እንጂ በሕዝብ መሀል እየሄዱ የምእመናን ሕሊና መስረቃቸው ምናቸውም አይደለም፡፡ ይህ ዕለት ዕለት የማየውን ነው የምነግራችሁ፡፡ ይህንን የሚያደርገው ደግሞ የቤተክርስቲያኒቱ ዘበኛ ነው፤ ዘበኛው ለወንጌል እና ለጸሎት የተሰቀሉ መብራቶች ለማጥፋት፣ የቤተክርስቲያን በር ለመዝገት የሚቸኩል እንጂ የቤተክርስቲያኒቱ ዓላማ የገባው አይደለም፡፡ ከኋላው ደግሞ ሰበካ ጉባኤ አለ ዘበኛው በቅዳሴ ሰዓት እየዞረ እንዲፈትሽ የታዘዘው፡፡ ሰባካውም ቢሆን የሙዳይ ገንዘብ የሚቆጥረው በሰንበተ ክርስቲያን እሑድ አይደለም እንዴ? ኧረ እንዲህ አይደለም! ሕዝቡ የመረጣችሁ ሰንበት እንድትሽሩ ነው እንዴ? ሥርዓተ ቤተክርስቲያን እንድታፈርሱ ነው እንዴ? ወይስ ሙስናን ለመዋጋት ለግልጽነቱ ብላችሁ ይሆን በሕዝብ ፊት የሙዳይ ገንዘብ የምትዘረግፉት?... ለመሆኑ ከቅዳሴ የሚበልጥ አለ እንዴ? ቅዳሴውስ የሰበካውን አባላት አይመለከትም? የእነሱ ይቅር በዕለቱ ቅዳሴ ለማስቀደስ የቆመውን ወጣት ገንዘብ ቁጠር እያሉ ጸሎት ያሚያቋርጡ በብዙ አብያተ ክርስቲያን ማየቴ ነው፡፡ ብነገራቸው አይሰሙም ሊማት ነዋ፣ ገንዘብ ብቻ! እስኪ መጀመሪያ ሕዝብ አስተምሩ አያንገብግባችሁ፡፡ ሕዝብ ካለ የምትንገበገቡለት ገንዘብ ከእነሱ ይገኛልና፡፡ አሁን አሁንማ መርሐግብራቱ የሚዘረጉት ገንዘብ ለመሰብሰብ ብቻ የሆነ ይመስላል፡፡ በቤተክርስቲያን አውደ ምህረት የሰዎች ሙገሳ፣ የገንዘብ ልመና፣ የሳይንስ እና የፖለቲካ መልእክት ማስተላለፍ የተለመደ ሆኗል፤ ነገር ግን መሆን የነበረበት በፖለቲካ መድረክ ቤተክርስቲያን  መልእክት ማስተላለፍ ነበረባት፡፡ ምን ይደረግ በዘረኞች እና በሆድ አደሮች ነገሩ ተቀያየረ እና ቤተክርስቲያን የበታች ኃላፊው ፖለቲካ ከበላይ ሆኖ መራት፡፡
ሌላው የሆድ አደሮች ስራ የሰንበት ትምህርት ቤት አወቃቀርን በእነሱ ልክ ማድረግ ነው፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤቱ ከሕዝቡ የተውጣጣ ሲሆን ቤተክርስቲያን ሲሄድ ግን ሰንበት ትምህርት ቤቱን እንዲያስተምር በተመደበው መምህር ልክ ይወሰናል፡፡ እሱን የማይመስሉ ቦታ የላቸውም ብሰበሰቡ እንኳን ይበተናሉ በመምህሩ፡፡ ተቀባይነት ለማግኘት ግድ መምህሩ የምናገረውን ቋንቋ መናገር፣ እሱ ከሚያውቀው ባህል የወጣ መሆን አለበት፡፡ እንዲህ አይነቱ ዬት ዬት እንደሆነ መገመት አያዳግታችሁም፡፡ በዚህ አይነት አመለካከት ያላችሁ የቤተክርስቲያን አገልጋዮች አንድ ቀን በእናንተ ላይ መድረሱ ስለማይቀር እስኪ ሁላችሁም ራሳችሁን ተመልከቱ፡፡ ዛሬ ዛሬማ የሰንበት ትምህርት ቤቱ አባላት ከሰበካ የተማሩትን ሥርዓተ ብልሹነት ይፋ እያወጡ ነው፡፡ በቅዳሴ ሰዓት ገንዘብ ማስገኛ ዕጣዎችን ማዞር፣ ባጠቃላይ ከዘረኝነት አንስቶ ሥርዓት አልበኝነት እየገነነ መምጣት አሳሳቢ የሆነ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ነው፡፡የቤተክርስቲያን አገልግሎት በአማርኛ ልክ የተሰራ ነው ሌላው ባእድ ነው፡፡ ግን መብቃት አለበት፡፡ ሌሎች ይቅሩ ከሀገሪቱ ክፍል የተወጣጡ ተማሪዎች የምስተናገዱባቸው በሀገራችን የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት እንኳን እንዴት ማሰብ አቃታቸው? ምክንያቱም ዘረኞች እና ሆድ አደሮች ስለሆኑ ነው፡፡ ለማስመሰል ግን በሕዝብ ቋንቋ አያስተማርን ነው የሚሉ በስተዋል፣ ላሁኑ ይለፈኝና እውነታውን ግን አላስቀርም በተለይ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ያለውን አገልግሎት ማስመሰሉ ቀርቶ በእውነት እስከሚሰራ፤ እንዳይማይፈለግ በማስረጃ የተደገፈ ስለሆነ ራሳችንን ብንመለከት፡፡ ሃይማኖታዊ መሆኑ ቀርቶ ፖለቲካዊ እንደሆነ ከተግባሩ ተረድተናል፣ የአገልግሎት ጥያቄ ሲጠየቅ ከፖለቲካ ጋር ማላከክ፤ማያያዝ፣ዘረኛ ማለት፣ ሊሰሟመቸው ለሚችሉ ሰዎች እና አካላት ጥያቄ አቅራቢዎቹን ማቅረብ (መረጃው በእጄ ስላለ) ሌለውም ብለዋል ግን ለዚህ ለባለቤቱ ለቤተክርስቲያን አምላክ እንስጥ፡፡ ብዙ ጊዜ ደግሞ ትምህርታቸው ስለ ተሀድሶ ነው ደግሞ ለራሳቸው ሳይጣን አምላኪዎች ሆነው፡፡ ዘረኝነት ሰይጣን ማምለክ ነውና፡፡ እስኪ መጀመሪያ ቤተክርስቲያኗ ዬት እንዳለች እንወቅ፣ ልታደም የሚችለውንም ሕዝብ እንለይ (እንወቅ) ከዚያ ሁሉም ነገር ቀላል ይሆናል፡፡ የሐዋርያት አምላክ ሁሉን ነገር ማስተካከሉ አይቀርም ነገር ግን በፍቅር እና በስምምነት ይሁን፤ የተስተካከለ ለት ግን የተጠላችሁ ትሆናላችሁ፡፡ በመሠረቱ ክርስቲያን ተዋደው የሚኖሩባት እንጂ ተቻችለው አይደለም፣ እንድንዋደድ እንድንደማመጥ ራሳችንን እናስተካክል፣ አመለካከታችንን እናስተካክል፡፡

ምድር ሁሉ አውሬውን ይከተላል- አሁን ካለው ጋር ሲታይ


እስኪ ከሁሉ አስቀድመን በዮሐንስ ራዕይ ላያ የሰፈረውን ምእራፍ 13 ከቁጥር አንድ እስከ ዘጠኝ ያለውን እናንብብ እርሶ ሙሉውን ምዕራፉን ያንብቡ፣ ዘመኑ ክፉ ነውና አውሬው በረቀቀ መልኩ ስልቱን ቀይሮ ትውልዱን ከክርስቶስ ለይቶ ለራሱ ለማድረግ እየሰራ ስለሆነ መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ የተከተልነውን፣ የወደድነውን፣ ልዩ ቦታ የሰጠናቸውን ሰዎችም ይሁኑ ድርጅቶች ወይም አካላት በምን መንፈስ እንደተከተልናቸው፣ እንደወደድናቸው መመርመር ያስፈልጋል፡፡ መንፈሱ በሁሉም ቦታ ይሰራል፣ የሃይማኖት ቦታዎችም ይሁኑ በፖለቲካ ስፍራዎች ወይም በሌሎች ቦታዎች ይሰራል፣ የሱ ዓላማ ቦታ መምረጥ ሳይሆን ሰውን ጠምዶ የራሱ ማድረግ ስለሆነ በማስተዋል እንጓዝ እላለሁ፡፡ መከተል የሚመጣው ከአባልነት ሲያልፍ ነው፡፡ ሕዝቡ ያ የሚከተሉት ሰው (አካል) ጓደኛ/አባል ለመሆን ከሚፈለገው ቁጥር በላይ ሲሆን ስርዓቱ መከተልን ብቻ ይፈቅድላቸዋል፡፡ ይህን በማኅበራዊ ድረ ገጾች ላይ እንደመለከታለን፡፡ መከተል መነሻው አንድ ሰው ወይም ድርጅት (በአንድ ሰው እንደሚቆጣጠር እንዳንረሳ) ላለው ጥሩ ነገር ለማግኘት ሲባል የምናደርገው ነው፡፡ መጨረሻው ግን መጪውን አውሬ ለመከተል እያደረግን ያለነው ልምምድ ነው፡፡
ዛሬም ሰዎች የዲያብሎስን ሀሳብ ስለሚፈጽሙለት አንዳንዶች በቀጥታ ሌሎች ደግሞ በተዘዋዋሪ አባሉ ወይም ጓደኛው ሆነውታል የአባልነት ወይም የጓደኝነት ቁጥርም ከመጠን በላይ ስለሆነ ካሁን በኋላ ያለው አማራጭ መከተል ብቻ ነው፡፡ ምክንያቱም ሰይጣን ከጥንተ ጀምሮ ሕዝቡን በብዙ የሠይጣን መንግሥት አሰራር (መዋቅር) ውስጥ ገብተው ይገኛሉ፡፡ ነገር ግን ‹‹ከኔ በቀር ሌሎች አማልክት አይሁንልህ›› ይላል የእግዚአብሐር ሕግ፡፡
ከጊዜያዊ ሰውን መከተል ጋር ተያይዞ፤ በፖለቲካ፣ በሃይማኖት፣ በሙዚቃ፣በሌላም…
የአውሬውን ምስል እንደሚጠቀሙ ባሁኑ ጊዜም የፖለቲከኛውን፣ የዘፋኙንም፣ የስፖርተኛውን…. ፎቶ መጠቀም ከአውሬው ዘመን ጋር ያመሳስላል፤ የሚገርመው ደግሞ ፎቶዎቻው የምንጠቀማቸው ሰዎች ከእግዚአብሔር ይልቅ ወደ ሰይጣን/ወደ ዓለም የቀረቡ ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ ታዋቂ ብለን የቆጠርናቸውስ በማን ዘንድ ነው? በዓለም ዘንድ ወይስ በቤተክርስቲያን ዘንድ? በሠይጣን ዘንድ ወይስ በእግዚአብሔር ዘንድ? መጪው አውሬውም ሕዝቡ እግዚአብሔርን ትቶ እሱን እንዲከተል ያደርጋል፡፡ ዛሬ የያዝነው ፎቶ ምንም እንኳን አፍ አውጥቶ ባይናገርም ከአእምሮ አልፎ ስሜታችንን ገስቶ መንፈሳችንን እንደተቆጣጠረ መዘንጋት የለብንም፡፡ በአውሬው ዘመንም ልክ እንደዛሬው ሰዎች የአውሬውን ፎቶ ይዘው በኪሳቸው፣ በቲሸርታቸው፣ በጃኬታቸው፣ በቤታቸው፣ በመኪናቸው እየለጠፉ ደጋፊ መሆናቸውን ይገልጻሉ፡፡ በቤታችን ካስቀመጥነው የቅዱሳን ስዕል እኩል ከተቀመጠ፣ የፌዝ ቡክ መለያ ስዕል የነበረውን የቅዱሳን ሥዕል ወይም የረሳችን ፎቶ ቀይረን በተከተልነው ሰው ወይም በአውሬው መተካት ስንጀምር አውሬውን መቀበላችን፣ በአእምሮአችን መሳላችንን ያሳያል፡፡ እያደረግን ያለነው ግን መጀመሪያውም ሠይጣን የነበረውን፣ ዛሬ ደግሞ መልኩን ቀይሮ ሌላ መስሎ የመጣ መሆኑን እንኳን እንዳንመረምር ጊዜ ሳይሰጠን በአጭር ጊዜ ውስጥ በሚያደርጋቸው ተአምራት እንድንከተለው እና እንድንደግፈው በማድረግ በዓለም አቀፍ ደረጃም ተከታዮቹን በመጠቀም የደጋፊነት ፍርማ የማሰባሰብ ስራ በማሰራት ለራሱ ያስገዛል ማለት ነው፡፡ ይህንን ማወቅ የሚቻለው በእውቀት ብቻ አይደለም፣ ፖለቲካ መተንተን ስለቻሉበት አይደለም መለየት የሚቻለው፣ የሃይማኖት እውቀት ስላለን አይደለም ይልቁን የእግዚአብሔር ፈቃድ ከጠየቅን ብቻ ነው፡፡ ይህ ማለት እየሆነ ያለው በአእምሮአችን ልክ ስንመዝነው ትክክል መስሎ የታየን፣ አስደሳች ነው ብለን የተቀበልነው ነገር እግዚአብሔርን አስደስቶታል ወይ? የሚለውን ማረጋገጥ ከቻልን ትክክል ነው፡፡ ሠይጣን ደግሞ ከመጀመሪያው እና ከሁለተኛው የማወቂያ መንገድ እንዳናልፍ ነገሮች በፍጥነት በቀናት እና በሳምንታት ቢበዛ በወራት በመስራት ከእግዚአብሔር የሆነ አስመስሎ ያቀርባል፡፡ በዚህ መሀል አድስ ነገር ሳይኖር የነበረውን በመተግበር አንድ ሰው ሳይቀር የተለየ ነገር የተሰራ በማስመሰል ሕዝቡ የአግዚአብሔርን ፈቃድ ሳይለይ እንዲከተለው ያደርጋል፡፡ የሚገርመው ግን ሕዝብ ሁሉ ለአውሬው ከሰገደ በኋላ ትክክለኛ እግዚአብሔር ሲገለጥ ሕዝቡ ሁሉ ለአውሬው ቃል ገብቶለት ወይም ፈርሞለት ስለ ነበር ወይም ከሱ ጋር ለመሆን ወስኖ ስለ ነበር ለእግዚአብሔር መሆን አይችልም፤ የእግዚአብሔር የሆኑ ነገሮችን በሙሉ መጠቀም አይችልም፡፡
ሰውን መከተል ምን አይነት ተጽዕኖ አለው? - ባርነት፣ መገዛት፣ በሰው ሀሳብ መመራት፣ የራስን አእምሮ እና ልብ አለመጠቀም፣ የተከተሉት የሆነውን ሁሉ መሆን፤ ከወደቀ መውደቅ፣ ከተሳሳተ መሳሳት፣ ካመነ ማመን፣ ከተቀበለ መቀበል፣ ከተቃወመ መቃወም፣ ከግል እምነት ወደ ቡድን እምነት ማድላት፣ ተስፋ መቁረጥ፣ ብቻ እግዚአብሔር የሰጠውን አእምሮ፣ ስሜት እና ልብ አለመጠቀምን ያመጣና ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚለይ ይሆናል፣ ሐዋርያት ህዝቡ ክርስቶስን እንዲከተሉ አደረጉ እንጂ እነሱን እንዲከተሉ አላደረጉም፣ (መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ራሱ ‹‹የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የአግዚአብሔር በግ እነሆ ነበር ያለው››)፣ ፍቅር ልብ ላይ ነው ማረፍያው፤ ልብ ላይ የሚያድረው ደግሞ እግዚአብሔር ነው- ታዲያ እኛ ልባችንን ለምድራዊያን ፖለቲከኞች እና ዘፋኞች ካሳደርን እግዚአብሔር አልተካደም ወይ?፣ ቅዱሳን አልተካዱም ወይ? ለመሆኑ እያደረግን ያለነው ነገር ትክክል ነው (አእምሮአችንን)፣ ያስደስታል (ስሜታችንን)፣ የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው፤ እግዚአብሔር ወዶታል (ልባችንን) በዚህ ሁሉ አረጋግጠን ነው ወይ እንዲሁ ሆ ብለን የተነሳነው? ያለ እግዚአብሔር ፈቃድ የሆነ ሁሉ እድሜው አጭር ነው ለሕዝብ ግን ታላቅ ሐዘን እና የልብ ስብራት ነው፡፡ ክርስቲያኖች አውሬው በምድር ላይ ተገልጦ ሕዝብ ሁሉ ቢከተለው እንደማይከተል ሁሉ አሁን ባለው ሁኔታ ግን አንድም ሰው የሚቀር አይመስልም፡፡
አውሬው የስምንት ሺህ ዓመት ልምድ ያለው በመሆኑ የተመረጡትን እንኳን እስከ ማሳት ይደርሳል፤ በምትሐቱ፣ በጥበቡ፣ በእውቀቱ እና በድርጊቱ፡፡የአግዚአብሔር እያስመሰለ፣ ከእግዚአብሔር የተቀባ በማስመሰል፣ ከእግዚአብሔር የሆነ በማስመሰል ሕዝብ እንዲከተለው በማድረግ ባልተከተለው ላይ ሕዝብ እንዲነሳበት ያደርጋል፡፡ ሠይጣን እና ተከታዮቹ በጭካኔ መንፈሱ ካልተሳካለት ትሕትና ወደሚመስል   የተመረጡት የተበሉት ጳጳሳት፣ ካህናት፣ መነኮሳትን፣ ዲያቆናትን፣ መምህራነ ወንጌልን፣ ማኅበራትን፣ ድርጅቶችን፣ በተለያየ መድረክ ተጽዕኖ ፈጣሪ ተብለው የታወቁትን ሲያስት ተከታዮቹ በሙሉ ይወድቃሉ፡፡ ይህ ሰይጣን ከምን ጊዜም በላይ ሕዝብን ለመጣል የሚጠቀምበት ሴራ ነው፡፡ ምንም እንኳን ጊዜው ቢደርስም፣ የአግዚአብሔር ፈቃድ ቢሆንም ጌታችንን አይሁድ እንዲይዙት ያደረገው በሱ ሞት መንጋው እንዲበተን ነበር፤ እውነትም በክርስቶስ መያዝ ከአንዱ በቀር ሌሎች ፍርሐት እና ድንጋጤ ይዟቸው ነበር፡፡ ሌሎችማ እነ ሉቃስ እና ቀለዮጳ ተስፋ ቆርጠው አምነው የነበሩትን ትተው ብርቱ ነብይ እንደ ነበረ አድርገው እያወሩ ወደ ኤማውስ መንደር ይሄዱ ነበር፡፡ አሁንም እየሆነ ያለው ከመንፈሳዊ ሊቃውንት እስከ ምእመን ድረስ ከእግዚአብሔር ይልቅ ሰውን የሚከተል፣ ሰውን የሚደግፍ፣ የዚህች ሀገር መፍትሔዋ ከቤተክህነት መሆኑ ቀርቶ ከፖለቲካ ዓለም ብቻ እንደሆነ በማሰብ ቤተክህነት ራሷ ፖለቲካን ወይም ምድራዊውን መንግሥት ብቸኛ መፍትሔ አድርጋ እንድትወስድ ማድረግ ቤተክርስቲያን ከጥንት ጀምሮ ይሰራ እንደነበር አሁንም ለአውሬው ለማስረከብ እየተሰራ ያለ ሴራ ነው፡፡ ምንም እንኳን እግዚአብሔር ስለተመረጡት አባቶች ባያሳካውም ቤተክርስቲያን እውቅና ሰጪ ሳትሆን እውቅና ጠያቂ ለመሆን እንድትሄድ የሚያደርግ አካሄድ እየተስተዋለ ነው፤ ይህ ደግሞ ለመጪው አውሬ ምቹ ይሆንለታል፡፡  

 ሰኔ 16/2010

Saturday, August 18, 2018

ዘረኝነት በቤተክርስቲያን


**** ዘረኝነት በቤተክርስቲያን ***
የተወደዳችሁ ክርስቲያኖች ከዚህ በፊት ሦስት አገንዳዎች ላይ ያለውን እውነታ ለመጻፍ ቃል ገብቼላችሁ ነበር እነዚህም
  1. ዘረኝነት በቤተክርስቲየን 
  2. በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በማኅበረ ቅዱሳን እና በኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪ ተማሪዎች መካከል ያለው እውነተኛ ችግር     
  3. የ666 አሰራር በቤተክርስቲያናችን የሚሉ ነበሩ፡፡ የመጀመሪያውን እነሆ ብያለሁ፡፡

…. ዘረኝነት በቤተክርስቲያን… ይህ ዘረኝነት የሚለው ቃል ከቤተክርስቲያን ጋር መነሳቱ ያሳፍራል፤ ምክንያቱም ስለማይስማሙ ነገር ግን የዚህች ቤተክርስቲያን ተጠቃሚው ሰው ስለሆነ ሰው የገባበት ደግሞ እንከን ስለማይጠፋው ከዚህ ቃል ጋር ልትነሳ ችላለች፡፡ የኔ ዓላማ ይህን የተጣበቀባትን መዥገር ከሷ አላቅቄ ባላት በሕርይ እና ዓላማ እንድተቀጥል ድርሻዬን ለመወጣት ነው፡፡ ሰው ዘረኛ ሆነ ማለት ከእግዚአብሔር ተለይቶ፣ ባሕርይውን አጥቶ ሌላ ሆነ ማለት ነው፤ ምክንያቱም የሰው ዘር አንድ ነው እሱም ሰው ነው፣ ዘረኛ ከሆነ ደግሞ ሌላ ፍጡር ሆነ እንደ ማለት ነው፡፡ ከክርስትና ጋር ደግሞ ምንም ዓይነት ሕብረት የለውም፡፡ ስለሆነም በቤተክርስቲያን ዘረኞች ከከርስቶስ ሳይሆኑ ከአባታቸው ከዲያብሎስ ናቸው፡፡
ሰው ዘረኛ መሆን የሚጀምረው ሰውነቱን ሲያጣ፣ ሰውነቱን ሲረሳ፣ ስጋዊ ጠባዩ ሲያይል፣ መንፈሳዊ ሕይወቱ ሲሞት ነው፡፡ ሰው ዘሩ አንድ ነው እሱም ሰው ነው፡፡ እግዚአብሔር ሦስት ዘሮችን ፈጠረ ይህ ማለት ልባዙ የሚችሉ ዘሮችን ማለቴ ነው፡፡ እነዚህም የሰው ዘር፣ የእንሰሳ ዘር እና የዕፀዋት ዘር ናቸው፡፡ ሰው እንግዲህ መጀመሪያ ተፈጠረ ከዚያ በኋላ ያችን የመጀመሪያዋን ዘር ሳይለቅ ከዚያች እየተወለደ እየበዛ ይኖራል፡፡ አሁን ላለው ሰው መነሻው አዳም እና ሔዋን ናቸው፡፡እስካሁን ድረስ አዳም እና ሔዋን እኛን ልጆቻችን ይሉናል፡፡ እኛ ተለያይተን የማን ልጆች ልንል ነው? ስለዚህ በመካከል ያለው ትውልድ ቢኖርም ባይኖርም እኛ ሁላችንም ወንድማማቾች ነን፡፡ ነገር ግን ይህ የሰው ዘር በበደለው በደል ሞትን ገንዘቡ አድርጎ ነበር አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ሕያው አድርጎናል ከዚህ ጋር ተያይዞ ምንም እንኳን በተለያዩ ምድራዊ ነገሮች ብንለያይም ክርስቲያኖች በኢየሱስ ክርስቶስ አንድ ነን፡፡ ይህ ደግሞ በመንፈስ ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ሰው ስጋ ብቻ አይደለም መንፈስም ነው እንጂ፡፡ ሰው ስጋ መሆኑን ብቻ ስያስብ ሁሉ ነገሮች ስጋ በሚፈልገው ብቻ ይራመዳል፡፡
እንግዲህ ሰው በሰማይ ካለው ከእግዚአብሔር ጋር ሕብረት የሚፈጥረው በመንፈሳዊ ባሕርይው ነው እንጂ በስጋዊ ባሕርይው አይደለም፡፡ ዘር መቁጠር የሚጀምረውም ይህንን መንፈሳዊ ለቆ ስጋዊውን ሲከተል ነው፡፡ ክርስቶስ በምድር ይህንን መንፈሳዊ አንድነት የሰጠን፣ የገለጠልን በቤተክርስቲያን በኩል ነው፡፡ በቤተክርስቲያን ሲባል ደግሞ ሦስቱን የቤተክርስቲያን ትርጉም መርሳት የለብንም ብዙዎቻችን ‹‹ቤተክርስቲያን›› ስንል በብዙዎቻችን አእምሮ የሚመጣው ሕንጻ ቤተክርስቲያን ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን ስህተት ነው፡፡ ሁሉም ትርጉሞች ሕንጻ ቤተክርስቲያን፣ የምእመናን ሕብረት እና እያንዳንዱ ምእመን መሆኑን ካልተረዳን ሳናውቅ በምድርም ሆነ በመሰማይ ካለችሁ ቤተክርስቲያን ሕብርት እንለያለን፡፡ ብዙ ሰዎች ከሊቅ እስከ ደቂቅ ቤተክርስቲያን ሲባል ሕንጻ ቤተክርስቲያን ብቻ መሆኑን ያስቡና ለጊዜው ከቤተክርስቲያን የሚያገኙት ገንዘብ (ደመ ወዝ) እስካለ ድረስ ምእመናን ከቤተክርስቲያን ሲጠፉ ምንም የማይመስላቸው ለዚህ ነው ፡፡ ነገር ግን ሦስቱም ካልተሟሉ አንድ ቀን ሁሉም ይጠፋሉ፡፡ ለምሳሌ እያንዳንዱ ምእመን ከሌለ የምእመናን ሕብረት አይመጣም፣ የምእመናን ሕበርተ ከሌለ ደገም ሕንጻ ቤተክርስቲያን የለም፤ ሕንጻ ቤተክርስቲያን ከሌለ ደግሞ ወደ ሰማይዊቷ ቤተክርስቲያን መቀላቀል/መሸጋገር የለም፡፡ ባሁኑ ጊዜ ኦርቶዶክስ ምእመናንን እያጠፋ ያሉት ይህንን ያልተረዱ ሆድ አደሮች ናቸው፡፡ የቤተክርስቲያን ባሕርያት የሚባሉ ቅድስት፣ አንዲት፣ ኩላዊት እና ሐዋርያዊት የሚባሉ ሲሆኑ ምእመናንም ይህን እንዲያሟሉ ነው፡፡ በቅድስት ባሕርይዋ ትቀድሳቸዋለች፣ በአንዲት ባሕርይዋ በመንፈስ (በክርስቶስ) አንድ ታደርጋቸዋለች፣ በኩላዊት ባሕርይዋ ምእመናን በሄዱበት ሁሉ ክርስትናቸው ያው ነው በጊዜ እና በቦታ አይለወጥም፣ በመጨረሻም ሐዋርያዊት ባሕርይዋ የምእመናን መመሪያቸው ጌታችን ያስተማረው፣ ሐዋርያት የሰበኩት ትምህርት እና ሕይወት ነው እንጂ እንግዳ የሆነ ትምህርት እና ሕይወትን አይከተሉም ማለት ነው፡፡ ስለዚህ የቤተክርስቲያን ባሕርያት በግልም ሆነ በሕብረት መሆን ያለባቸውን ትናገራለች፡፡ ማንኛውም ክርስቲያን ጳጳስ ሆነ መነኩሴ፣ ቄስ ሆነ ዲያቆን፣ መምህር ሆነ ምእመን ይህንን ባሕርዋን የማያከብርላት ከሆነ ወደ እግዚአብሔር መንግስት መግባት አይችልም ምክንያቱም ቤተክርስቲያን ከባሕርይዋ ጋር የሚስማማውን ብቻ ወደ ላዩ መንግስት ወደ እግዚአብሔር ታሸጋግራለችና፡፡ ቅድስት ቤተክርስቲየን በሰማይ ያለውን ወክላ በምድር ያለች ናት እንጂ ምድራዊ ሆና አይደለም፡፡ ከዚህ ዓለም እይታ ውጪም ናት፤ በሀገራችን እንኳን ምድራዊ አለመሆኗን እንድንረዳ የተሰወሩ አብያተ ክርስቲያናት እና ገዳማት አሉን አይደል እንዴ? ስለዚህ በቤተክርስቲያናችን ይህን ባሕርይዋን የሚጠብቅላት ወይም ይህን ባሕርይዋን የሚያሟላውን ሰው ብቻ ትቀበላለች፡፡ ይህን የማያሟላ በውስጧ ቢኖሩም እንኳን ወደ ላኛይቱ ቤተክርስቲያን እንዲገባ የሚያደርገውን ሸኚ ደብዳቤ አትሰጠውም፤ ለጊዜው ግን ዝም ብሎ ይኖርባታል፤ ሁሉም ያለባት የኖኅ መርከብ ናትና (ሰውም፣ እንሰሳም፣ ርግብም፣ ዘንዶም… አለባትና)፡፡ ጠንቋይም ይሁን አስጠንቋይ፣ ሙስኛም ይሁን ሆዳም፣ ዘረኛም ይሁን ጠባብ እንደ ኖኅ መርከብ ሁሉንም ችላ ታቆያለች፡፡
ለጊዜው ለዘመናት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያናችን ከውጪው ይልቅ የውስጥ ችግር ሆኖብን የውጪው አካል እስከሚሰማብን ድረስ ከቤተክርስቲያናችን የማይጠበቀውን ነገር በማድረግ ስንባላ፣ ተኩላው ከነጣቃቸው ይልቅ እኛ ራሳችን በአፉ የሰጠነው የነፍሳት ብዛት፣ክርስቶስ የሰጠንን ቤተክርስቲያን ባሕርይዋን ዘንግተን የውስጥ ከሀዲዎች የሆን፣ ኃያልነቷን አውድመን የበታች ያደረግናት፣ ኢትዮጵያን ያስከበረች እና ነፍስ የዘራችባት ቅድስት ቤተክርስቲያን ዛሬ ግን በገዛ ልጆቿ ስትቦጠቦጥ መዥገር ሲሆኑባት፣ ሁሉ ያላት ደሀ መስላ በልጆቿ ተራቁታ ማየት ያሳዝናል፡፡
ቤተክርስቲያን እንደ ባሕርያዋ ሰው የሆነ ሁሉ የተጠመቀ በክርስቶስ ያመነ ሁሉ የሚኖርባት ናት፡፡ አማራ፣ኦሮሞ፣ ትግሬ፣ ወላይታ… ጥቁር፣ ነጭ … ሳይባል፡፡ ምክንያቱም ባሕርይዋ ሁሉንም የመቀበል አቅም አለውና ‹‹ከምፓተብል›› ነው ማለት ነው፡፡ ኢትዮጵያ ሀገራችንም እንዲህ ናት 80 ብሔር ብሔረሰብ በቋንቋ በቀለም፣ በባህል፣ በአኗኗር ብለያይም በኢትዮጵያዊ አንድ ሆኖ ይኖራል አንድነታቸውም በኢትዮጵያዊነታቸው እንጂ ልክ እንደ አጼ ኃይለሥላሴ ዘመን በአንድ ቋንቋ ተናገሩ አይባሉም፣ ይልቁን ከስጋዊ ሀብታቸው ይልቅ በመንፈሳዊ ሀብታቸው ኢትዮጵያን በልባቸው/ በመንፈሳቸው ይዘው በአንድነት ይቆማሉ ጠላት በፈለገው አቅጣጫ ሲመጣባቸው ወጥተው ድል ያደርጉ ነበር ዛሬም የውስጥ እንጂ የውጭ ጠላት ባይኖርባትም፤ የውጪው ጠላት የውስጥ ጠላት ፈጥሮ ሄዷላ፡፡ ቅድስት ቤተክርስቲያንም ለሁሉም የሚስማማውን ባሕርይዋን ሳትለቅ ለሁሉም በሚሆን መልኩ የተሰጠች ናት፡፡ ለምሳሌ ክርስቶስ ይህችን ቤተክርስቲያን ለዓለም ከመግለጡ አስቀድሞ የማዳኑን ስራ ሰርቶ ወደ ሰማይ አርጎ፣ ደቀ መዛመርቱን ኃይል  አስኪለብሱ በኢየሩሳሌም እንዲቆዩ አዝዞ፣ በአስረኛው ቀን መንፈስ ቅዱስን ሲሰድላቸው ኃይልና ጥንካሬን፣ ሰማያዊ ኃይል ከታጠቁ በኋላ በምድር ያለውን ሕዝብ እንዲያገለግሉ የሕዝብ ቋንቋ ገለጠላቸው፡፡ ቤተክርስቲያን ማለት ደግሞ ይህች ናት፡፡ ከዚህ ውጭ የሆነች ቤተክርስቲያን ከክርስቶስ አይደለችም ወይም ሆድ አደሮች የተሰገሰጉባት ናት፣ ጽዳት ያስፈልጋታል፡፡ በሀገራችንም እስካሁን ድረስ የኃይለሥላሴ ሴራ ከቤተክርስቲያን ያልለቀቀን ይመስለኛል፣ ምክንያቱም ቤተክርስቲያናችን በአንድ ቋንቋ በአማርኛ ብቻ ተናገሪ የተባለች ትመስላለች፡፡ ስጀመር በተለይ በኃይለሥላሴ ዘምን ከእንግሊዝ ንግስት ጋር በነባራቸው ምስጢራዊ ሴራ ቤተክርስቲያንን የማስፋፋት እና የማጥፋት ሴራ ነበራቸው፡፡ ለዝያ ነበር አማርኛ ከሚችል ውጪ ሌላው ከቤተክርስቲያን አገልግሎት እንዳያገኝ፣ አገልግሎት እንዳይሰጥ ይደረግ የነበረው፡፡ … ታዲያ ይህ አዚም ዛሬ እኛን ለቆናል እንዴ? ከመናፍቃን የሚያንስ ስራ አይደለም እንዴ የምንሰራው? ይህች ሃይማኖት የአማራ ብቻ መስላ እንድትታይ አላደረጋትም እንዴ? ዛሬ ኦሮሚያ ክልል ላይ ላለው የሃይማኖት ውዥንብር መንስኤው ይህ አይደለም እንዴ? ሰፊው የኦሮሞ ሕዝብ ይህችን ሃይማኖት ጠልቶ ወደ እስልምና፣ ወደ ዋቄፈታ፣ ወደ ፕሮቴስታንት እንዲገባ ያደረገው ምን ይመስላችኋል? ዘረኞቹ ይህችን ኦርቶዶክስ ሃይማኖት የአማራ ብቻ መስላ እንድትታይ በማድረጋቸው አይደለም እንዴ? ከዘመን ብዛት የኦሮሞ እና ሌላውም ሕዝብ እስከሚጠራጠር ድረስ አልደረሰም ወይ? የሁሉ ሆና እያለች የአንድ ሕዝብ ብቻ የመሰለች ቤተክርስቲያን ሰማያዊ ሳይሆን ምድራዊ አደጋ እየደረሰባት ነው፡፡ ለምሳሌ በኦሮሚያ ክልል ያለች ቤተክርስቲያን በሕዝብ ቋንቋ ባለማስተማሯ በሕዝቡ ዘንድ የተለየ አመለካከት ፈጥሮባታል የባሌውን እና የሶማሌን እንዳትረሱ፣ በሌላ ቦታም የማይቀጥልበት ዋስትና የለንም፤ ምክንያቱም እንዲህ እንዲሆን ያደረጉ ዘረኞች ስለሆኑ ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ሕዝባዊ ካልሆነች ከባሕርይዋ ጋር የማይስማማ ፈተና ይገጥማታል፤ ድሮ ቤተክርስቲያን ክርስቶስን ለመስበክ ብላ ነበር ሰማእትነት የምትቀበለው ዛሬ ግን በአነዚህ ክልሎች ሕዝብ ውስጥ ባለመግባቷ ነው የምትፈተነው፡፡ የኦሮሞ እና የሶማሌ ሕዝብ ክርስትናን ተምሮ ቢቀበል ኖሮ ቤተክተርስቲያን ይቃጠላል እንዴ? ክርስቲያኖችስ በከንቱ ይሞታሉ? ከላይ እንደገለጽኩት በኢትዮጵያ ውስጥ በኃይለሥላሴ ዘምንም ሆነ ባሁኑ ጊዜ ያለው ሁኔታ ኦርቶዶክስን እያሰፉ ማጥፋት ነው የሚላችሁ ይህንን ነው፡፡ የኦሮሞ ሕዝብ ደፍሮ ኦርቶዶክስ የኔ ናት እንዳይል ተደርጓል፣ በታሪክ በመጡ ጫናዎችም ይሁን አሁን ባለው ሁኔታ የዚህ ሕዝብ ሃይማኖት አትመስልም፤ ምክንያቱም ሕዝቡ ባለበት ሕዝቡ በሚሰማ ቋንቋ እና እንደ ባህሉ የሚያስተምራት የወንጌል ስርጭት መዋቅር አልተዘረጋላትም፡፡ ይህንን ሲያጣ ሕዝቡ በእንግዳ ሃይማኖት መነጠቅ ሆነ፡፡ ባጠቃላይ የቤተክርስቲያናችን አገልግሎት በአማርኛ ላይ ማተኮሩ በኦሮሚያ እና በሌሎች ክልሎች ተስፋፍታለች ግን መሬት እንዳትይዝ ሆናለች ምክንያቱም ሕዝቡ አልታቀፈም፡፡ ይህ ከመሠረቱ የዘመናት የፈረንሳይ፣ የእንግሊዝ እና የጀርመኖች ድብቅ ሴራ ነበር ኦርቶዶክስን የአማራ ብቻ አድርጎ ማሰብ፤ የኛዎቹም፣ እኛም አራገብንላቸው፣ እኛ ብቻ ክርስቲያን የክርስቲያንን ሕይወት ሳይኖሩ፣ የቤተክርስቲያንን ባሕርያት እና ዓላማዋን ሳያሟሉ በስጋዊ ደስታ ብቻ ክርስቲያን መሆን አይቻልም፡፡
ስለዚህ ባሁኑ ጊዜ በሰው አእምሮ ያለው ይህችን ቤተክርስቲያን በዘር መድቧት እኛ ብቻ ካላገለገልናት፣ ካልተገለገልንባት ወዘተ የሚሉ በዚህ ዘመን የበዙበት በመሆኑ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የዘረኝነት በሽታ እንዲራገብ ምክንያት እንድትሆን ያደረጓት ዘረኞች አሉ፡፡ ቤተክርስቲያን ባላት ባሕርያት ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን ዘረኝነት ማጥፋት ትችላለች፤ ካልሰራች  ወይም በዘረኞች ከተሞላች ግን ለዘረኝነት መስፋፋት ምክንያት ትሆናለች፡፡ በዚህ አጋጣሚ ሁለተኛ አጀነዳዬን እስከማቀርብ ድረስ በዩኒቨርሲቲ ያላችሁ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች እና ያለአግባብ በዘረኝነት በሽታ የተጠቃችሁ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት እያሰባችሁበት ቆዩ፡፡ በቤተክርስቲያን ደረጃም ይሁን በሌሎች ቦታዎች ያለውን ችግር በግልጽ እየተነጋገርን በፍቅር አብሮ ለመኖር፣ ከሐሜት እና ከሐሰት ነጻ ሆነን ለማገለግል እና ለመገልገል በመካከላችን ያለውን ስውር የሠይጣን ሴራ አጋልጠን ቤተክርስቲያንን በማዳን ላይ ድርሻዬን ለመወጣት ነው፡፡ በዚህም እውነትን ተነጋግረን ሁሉም የራሱን ጥፋት አውቆ ወይም እንደታወቀባት ተረድቶ አደብ እንዲገዛ ለማድረግ ነው የኔ ዓላማ፡፡ በዚህ መሠረት ከሰማሁት፣ ካየሁት እንዲሁም ከደረሰብኝ ተነስቼ በቤተክርስቲያናችን ያለውን የዘረኝነት በሽታ በሚቀጥሉት የቤተክርስቲያን አገልጋዮች የምንጸባረቀውን እገልጣለሁ፡፡      
ካህናት
 ካህን ማለት አገልጋይ ማለት ነው፡፡የሚያገለግለው ደግሞ በክርስቶስ ያመኑ ምእመናን በሙሉ ነው፡፡ አንድ ሰው ካህን ሲሆን ምድራዊ ዜግነቱን ያጣና ሰማያዊ ይሆናል፡፡ ለአገልግሎቱ ደሞዙን የሚያገኘው ከእግዚአብሔር ነው፡፡ ሕዝቡ የእግዚአብሔር ገንዘብ ይሆነውን አስራት ይከፍላል፤ ካህኑ ደግሞ ያንን ይመገባል፤ ይህ  ነው ሥረዓቱ እንደ ዛሬ በሙስና አልተጨማለቀም፡፡ (እውነተኛ ካህናትን አይጨምርም)፡፡ ለካህን ሁሉ ዘመዱ ነው፣ በምድር ያለውን የሕዝብ ክፍፍል አይመለከትም፤ ይህን ማየት ከጀመረ የእግዚአብሔር ዓይን መባለ ቀርቶ ተራ ምእመን ይሆናል ምክንያቱም የእግዚአብሔር ዓይኖቹም አታዳላማ፡፡ አሁን ያለው ግን የአማራ፣ የኦሮሞ፣ የትግሬ… እየተባለ መለያየት ሆኗል፡፡ ይህ አብዛኛው የሚታየው ከሰሜኑ የሀገራችን ክፍል በሚመጡ ካህናት ላይ ይንጻባረቃል፤ አብዛኞቹ ባላቸው ክህነት ለማገልገል ሳይሆን ምድራዊ ኑሮአቸውን ለመምራት ነው ወደ ኦሮሚያ፤ ደቡብ እና ሌሎች አከባቢዎች የምንቀሳቀሱት፡፡ በሄዱበት የሕዝቡን ቋንቋ ከመልመድ ይልቅ በሚችሉት አማርኛ መቀጠልን ይመርጣሉ፡፡ ይህን ለማድረግ አማርኛ የሚችለውን ብቻ እየተከተሉ ይቧድናሉ፡፡ እውነት ለመናገር ብዙ ዘመናት በአከባቢው እየኖሩ የሕዝቡን ቋንቋ መልመድ አይፈልጉም፡፡ ይህን የምታነቡ ብዙ ነገር የተነጋገርን ሰዎች ስላላችሁ አስታውሱ እና ራሳችሁን ተመልከቱ፡፡
የካህን እና የሴት እንግዳ የለም ይባላል፤ ዛሬ ግን የካህን እንግዳ አለ በተለይ በኦሮሚያ ክልል፡፡ ካህኑ የመጣው ከሰሜን አከባቢ ስለሆነ ኦሮምኛ አይችልም፣ ሕዝቡ ደግሞ ከካህን ብዙ ነገር ይፈልጋል፤ ንስሀ እንኳን በአስተርጓሚ የሚሰጥበት ቦታ አለ፤ ይህንን የሚያደርጉት ኦርቶዶክስን አንለቅም ያሉ ሰዎች ብቻ ናቸው ሌሎችማ ሙስሊም፣ ፕሮቴስታንት፣ ዋቄፈታ ሆነዋል፡፡ የድቁና እና የክህነት ትምህርት እንኳን ለአንዳንድ ካህናት ከአማራ እና ከትግሬ ውጭ የሚሆን አይመስላቸውም፡፡ ሲያስተምሩም ከዘራቸው ብቻ ነው፤ ለእነሱ ተተኪ እያፈሩ ነው፣ ለኔ ግን ቤተክርስቲያንን እያጠፉ ነው ምክንያቱም የአከባቢውን ምእመን የቤተክርስቲያን ባእድ እያደረጉ በባእድ ምድር ደግሞ ቤተክርስቲያን ትኖራቸለች ማለት ዘበት ነው፡፡ ለምሳሌ በኦሮሚያ ክልል ኦሮሞ ሆነው ድቁና ሲማሩ የሚደርስባቸውን ጫና ዲያቆናቱ እና ካህናቱ ምስክር ናቸው፡፡ እነዚህ ካህናት ይህንን የሚያደርጉበት ምክንያት አንደኛ የሃይማኖት እውቀት ስለሌላቸው ሁለተኛ በታሪክ የመጣ የዘር ጥላቻ ስላለባቸው፣ሶስተኛ ፖለቲካዊ አስተሳሰብ ስላለባቸው ዐራተኛ በአከባቢው ያሉ ምእመናን የክህነት ፀጋ እና የመምህርነት ደረጃ ከደረሱ ቦታ እናጣለን በሚል ስጋት ይህንን ያደርጋሉ አይደለም እንዴ? ይህ በሕዝቡ ዘንድ ስር የሰደደ የዘረኝነት በሽታ አምጥቷል፡፡ ይህ ሐሰት ነው ካላችሁ የ2009 ሐመር የመስከረም የጥቅምት እና የህዳር መመልከት ይቻላል፡፡ እንዲሁም በዱላ እታና የተሰራ ጥናት አመላካች ነው፡፡እንደኔ ግን ካህናት የቤተክርስቲያኒቱን ሕግ እና ደንብ ተከትሎ መሆን እንዳለ ሆኖ ከአከባቢው ካህን ማፍራት ካልተቻለ ከጊዜ በኋላ በእድሜም ይሁን በሌሎች ምክንያት ካህናት ስንቀሳቀሱ ቤተክርስቲያን መዘጋቷ አይቀሬ ነው፡፡ አስታውሳለሁ እኔ ባደኩበት ካህናት ከአከባቢው፣ እዛው ተወልደው ያደጉ ስለሆነ ጡረታ እስከሚወጡ ብዙ መንግስታትን አሳልፈው እስከዛሬ ቆመው ሲቀድሱ፣ ዲያቆናት እና ካህናትን እያፈሩ በትክክል እያገለገሉ ያሉ አሉ፡፡ አሁን ያለው በተለይ በከተማ ያለው ክህነት ለገንዘብ ብቻ ሆኗል፤ ሥርዓት እየጠፋ በረከትን አርቋል፡፡
የካህናቱ ዘረኝነት ከብሔርም ወጣ የምልበት ጊዜ አለ፡፡ አሁንም ያያለው በኦሮሚያ ክልል ነው፡፡ ከሰሜን የመጡ ካህናት የጎንደር፣ የጎጃም፣ የትግሬ እያሉ የሚከፋፈሉም አሉ፡፡ ይህ ደግሞ ሁለተኛው ስግብግብነት ነው፣ ቤተክርስቲያኒቱን ከስር ፈንግሎ መጣል ነው፡፡ ይህ በዚህ እንዳለ የክልሉ ተወላጆች የአግልግሎት ጥያቄ ሲጠይቁ የአከባቢውን ሕዝብ ዘረኞች ማለት፤ አለማወቅ እና አለመቀበል ነው እንጂ ዘረኞቹስ እነሱ ናቸው፤ ክርስቶስ ያለውን ሳያሟሉ ክህነት የለም፡፡ ብዙ ጫናም ይደርስባቸዋል፣ ከፖለቲካ ጋር ያይዙባቸዋል፡፡ በከፍተኝ ትምህርት ተቋማት የኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪ ተማሪዎች እና የማኅበረ ቅዱሳን ግጭትም ምንጩ ማኅበረ ቅዱሳን ውስጥ የተሰገሰጉ የእነዚህ የዘረኞች ችግር ነው፡፡ እሱን በቦታው አነሳለሁ፡፡
መሆን ያለበት ከሰሜንም ይሁን ከሌላ ቦታ ካህናት ወደ አንድ ቦታ ስንቀሳቀሱ ህዝቡን ማወቅ ቶሎ ወደ ሕዝብ መግባት፣ በምድር በሚቻለው ሕይወት ጋብቻ፣ ክርስትና አባት፣ ማኅበር፣ እድር እና በመሳሰሉ ነገሮች ሕብረት ፈጥረው መኖር ለክህነታቸው ክብር ለስጋቸው እረፍት ነው፡፡ የአካባቢው ሕዝብ ዲያቆን፣ካህን ከሆነ፣ በሚሰማ ቋንቋ የእግዚአብሔርን ቃል ከሰማ በመንፈሳዊ ሕይወት አድጎ በማንኛውም መልኩ አጠገባችሁ ይቆማል፣ ለቤተክርስቲያን ከእናንት ይልቅ የሚደርስላት ይሆናል፡፡ ካልሆን ግን የሆነ ቀን ለዝያ አከባቢ እንደመጤ መቆጠራችሁ ቤተክርስቲያንንም ማስጠቃታችሁ አይቀርም፡፡ እውነተኞች ካህናት ግን አንዲህ አያደርጉም አነዚህ ከመጀመሪያውም ለሆዳቸው እንጂ ለክርስቶስ አልተሰማሩም፡፡ ማሳያውም ከካህነት የማይጠበቀውን ተግባር ሲፈጽሙ ይታያሉ፤ የአጋንንት ትምህርት ለመከላከያ ብለው ጥንቆላ፣ መተት፣ አስማት…. ይሰራሉ፡፡
መምህራን/ሊቃውንት
 በሁለተኛ ደረጃ ማንሳት የሚፈልገው መምህራነ ወንጌልን ነው፡፡ እንደ ቤተክርስቲያናችን ሥርዓት ካህናትም ትልቁ ስራቸው ወንጌል ማስተማር ቢሆንም ከግራኝ አህመድ ወዲህ ግን ካህናት እና ዲያቆናት ውዳሴ ማርያም፣ መልክአ መልክን፣ ቅዳሴን መሸምደድ ማዜም እና ዳዊትን መድገም፣ ቅዳሴውን በግእዝ እና በአማርኛ መቻል ብቻ የሆነ መስሏል፡፡ ይህ ቤተክርስቲያናችንን እጅጉን ጎድቷታል፡፡ የክህነት እድሜውም እንዲሁ ለቤተክርስቲያናችን ሥርዓት መፋለስ ትልቁን ሚና ተጫውቷል፡፡ የሊቃውንት ነገርም ከካህናት የተለየ አይደለም፣ በክርስቶስ ሐዋርያት የተመሰሉ ሊቃውንት ቤተከርስቲያን እውቀት ችግር የለባቸውም የሕዝብን የማወቅ ችግር እንጂ፡፡ ዘረኛ እንዲሆኑ ያደረጋቸው እነሱ የሚችሉትን ቋንቋ የሚችለውን ሕዝብ ብቻ እየፈለጉ ማስተማር ሌላውን ለማስተማር ዝግጁ አለመሆናቸው ነው፡፡ ከዚያ ውጪ ያለውን ምእመን እንደ ዘረኛ መቁጠር፤ ባለመስማቱ ከቤተክርስቲያን ወጥቶ ሲሄድም አለመንቃት ዘረኛ ያስብላቸዋል፡፡ ብዙዎቻችን የተሸወድነው እዚህ ላይ ነው፡፡ በክልሉ ያለው ሕዝብ ቤተክርስቲያንን ጥሎ ሲሄድ ምንም የማይሰማን ነገ ለዚህች ቤተክርስቲያን አደጋ እንደሆነ አለማወቃችን ነው፡፡
ምእመናን
ምእመናን ዘንድም የማያው ከካህናት እና ከመምህራኑ የተለየ አይደለም፡፡ ኦርቶዶክስ መሆን የሚችል አማራ ወይም ትግሬ የሆነ ብቻ የሚመስላቸው አሉ፡፡ ለምሳሌ ለአማራው ሕዝብ ኦሮሞ ማለት ሙስሊም፣ ዋቄፈታ፣ ፕሮቴስታንት እና ሌላ የሆነ ይመስላቸዋል፤ ክህነታቸው እንኳን የሚሰራ አይመስላቸውም፡፡ ይህም ታሪክን ያለማወቅ ነው፡፡ ኦሮሞም ቢሆን ሃይማኖት ውስጥ የተጫወታው ሚና ነበረው … እንዴት ሆኖ ነው ሃይማኖቱ ሌላ ሊሆን የሚችለው? ባለመማሩ ነው የሌላ እምነት ተከታይ ያደረገው እና ያስመሰለው እንጂ ሃይማኖቱስ የአባቶቹ የኩሽ እና የመልከጼዴቅ ሃይማኖት ነው፤ ሰፊ እና ሥርዓት ያለው ሕዝብ ነው፡፡ ግን ምን ይደረጋል በዘረኞች እና በሆድ አደሮች ለዚህች ሃይማኖት ባዳ ሆኖ መኖር ሆነ፡፡ ይህንን ተከትሎ ሌሎቹ ኦሮሞ ሙስሊም ነው፣ ኦሮሞ ፕሮቴስታንት ነው፣ ኦሮሞ ዋቄፈታ ነው እያሉ እኛ ዘረኞቹ ሳንረዳ በቀደድነው ገብተው እውነት የሚመስል ወሬ እያወሩ ሕዝቡን አናወጡት፡፡ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪ ተማሪዎች ያንገበገባቸው ሌላ ቦታ የማይገኙ ተጽእኖዎች ስላሉባቸው ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም በውስጡ የተሰገሰጉ ዘረኞችን ካላጠራ አደጋ እንደሚሆን ከወዲሁ ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ ግልጽ ማሽረጃዎች ስላሉ እውነት መደበቅ አይቻልም፡፡
ስለዚህ በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል ያላችሁ ምእመናን ኦርቶዶክስ መሆን የሚችል እናንተ ብቻ፣ ለዚህች ቤተክርስቲያን ብቸኛ ተቆርቋሪ፣ ከመሰላችሁ ገና ክርስትና አልገባችሁም፣ የልማድ ኑሮ ነው የምትኖሩ ማለት ነው፤ ይህን ከመሬት ተንስቼ አይደለም ያየሁት እና ያጋጠመኝ ስለሆነ ነው፡፡ የሚገርመው ደግሞ እንደዚያ ብለው ከሚያስቡ ሰዎች የክርስትና ጠረን አለማየቴ እና ፍጹም የሆነ ዘረኞች መሆናቸው ነው፡፡ ከሌሎች ክልሎች በተለይ ከኦሮሚያ (ኦሮሞ የሆናችሁ) ክርስትና የአማራ ሕዝብ ብቻ ነው ብላችሁ አስባችሁ በዚህች ቤተክርስቲያን እንደ ሁለተኛ ዜጋ ራሳችሁን የምትመድቡ ከሆናችሁ የክርስቶስን ዋጋ በዶ አደረጋችሁ ማለት ነው፡፡ እንደዚያ የሚያስቡ ሰዎች ብታዩ ቤተክርስቲያንን የማይወክሉ እና ቤተክርስቲያኒቱን እያፈረሱ እና ክርስትናን ለማጥፋት የምንቀሳቀሱ እንደሆኑ አውቃችሁ ድርሻችሁን ልትወጡ ያስፈልጋል፡፡ ይህን ባታደርጉ ግን እግዚአብሔርን የሚፈራ የአባታችሁ የኩሽ እና የመልከጼዴቅ ልጆች ልትባሉ አትችሉም፡፡ መልከጼዴቅ የጌታ ምሳሌ የተባለ/ሆኖ በስውር መስዋእት ይሰዋ የነበረ፣ የክርስቶስን መምጣት ይጠባበቅ ነበር፡፡ አንተ እንዴት ከሱ ሃይማኖት ውጪ ትሆናለህ? ከማን የተማርከውን ሃይማኖት ነው የምትከተለው? ከሕገ ልቡና ተነስ፣ ሕግ ኦሪትንም አስተውል ከዚያም ሐደስ ኪዳንን ቃኝ ለዚህች ቤተክርስቲያን ይበልጥ ደግሞ ለዚህች ሀገር ባለውለታ መሆንህን እንዴት ተዘነጋለህ፣ ዛሬ ኦሮሚያ ብቻ ብለህ ራስን የወሰንክ ሌላውስ የማን ሊሆን በኢትዮጵያ ጉዳይ ቀዳሚ ድርሻ ይኖረሀል፡፡ ኢትዮጵያ ካልክ ደግሞ ኦርቶዶክስ ትመጣለች፣ ስለዚህ ወንድሜ በዘረኝነት ምክንያት ርቀህ የቆምክ ይህች ቤተክርስቲያን ያንተ ናትና እግዚአብሔር በፈቀደልህ ፀጋ በሙሉ ተሳተፍ፣ ሃይመኖቱ የአንድ ብሔር አይደለም የሁሉም ሕዝብ ናት፡፡ ምናልባት ይህችን ቤተክርስቲያን ለሆዳችሁ ብቻ የምትጠቀሙባት ሰዎች ላያገባችሁ ይችላል፡፡  
በመጨረሻም ዘረኝነት ማለት ሌሎችን እንደ ራስህ አድርጎ አለመውደድ ነው፡፡ አንተ እያገኘ ያለኸውን እንዲያገኙ አለማሰብ ወይም እንዲያገኙ አለማድረግ ነው፡፡ ለሰው የምታስበው ደግሞ በመንፈሳዊ እና ስጋዊ ነው፡፡ እሱ ያለውን ትተህ አንተ ባለኸው ብቻ ልትደርስለት የምታስብ፣ የምትናገር ወይም የምታደርግ ከሆነ አንተ ዘረኘ ነህ፡፡ ስለዚህ ኢትዮጵያውያን ‹‹ኢትዮጵያ›› ገና ብለህ ስሟን ስትጠራ በአእምሮህ ውስጥ 80 ብሔር (ነገድ) የማይመጣ ሆኖ አማራ፣ ኦሮሞ…. ወዘተ ብቻ በአእምሮህ የሚያቃጭል ከሆነ አንተ ዘረኛ ነህ፡፡ እኛ ግን ብዙ ጊዜ እንድያመቸን ብለን (በስጋዊ) አንድ ያደረግን መስሎን ወደ መጨፍለቅ እንሄዳለን፡፡ ስለ አንድነትም ብናወራ ደግሞ ደስ ይለኛል፤ ምክንያቱም አንድነት ብለን የምናወራት በትክክል ካልተረጎመች ዘረኝነትን ትወልዳለች፤ ወልዳለችም፡፡ ምክንያቱም በኢትዮጵያ እና በክርስትና አንድነት ማለት እንደ አጼ ኃይለሥላሴ ዘመን አንድ ቋንቋ አማርኛ  መናገር አይደለም፡፡ ጌታችን ሐዋርያትን በዚህ መልኩ አይደለም ያሰማራቸው፣ በሕዝብ ቋንቋ ነበር ያሰማራቸው፡፡ ሐዋርያት አስራ ሁለት ሆነው ከምድር ያሉ ያሉ ሕዝቦችን አልፈው በብሔር ሕያዋን ያሉ ሰዎችን ማስተማር ችለዋል፡፡ እኛ ግን በሺህ የሚቆጠሩ ሊቃውንት ይዘን በዘረኝነት በሽታ ስለተያዝን ሕዝብ እና እኛ ሳንገናኝ በያዝነው እውቀት ፍሬ ሳናፈራበት ወደ መቃብር ሆነ፡፡ አሁን አሁንማ ያሳፍራል ቤተክህነቱ በዘር ተጨማልቆ ገዳማቱ ተረስተው፣ ከእግዚአብሔር ተስፋ ቆርጠን ምድራዊ ፖለቲካ ቤተክርስቲያናችንን እንዲያስተካክልልን ሰጠነው፡፡ ለመሆኑ ፖለቲካው ምናልባት የሚታየውን የቤተክርስቲያኒቱን አካል ማስተካከል ቢችል ሰፊውን የቤተክርስቲያን ክፍል ማስተካክል ይችላል?? በፍጹም፡፡ ስጀመር ለኔ አድስ ነገር የለም፤ ያው ያደረገውን ነው መልሶ ያደረገው፡፡ ወሰደ መለሰ፣ አባረረ መለስ፣ ለያየ አገናኘ… እናስተውል፡፡ ለዚህ ሁሉ የሚያነቡ ድንቅ የሆኑ አባቶች፣ የተሰወሩ ጋዳማት አሉን፡፡ የእንግሊዝ፣ የአሜሪካ፣ የጀርመን ባጠቃላይ የሰይጣኑ ዓለም፣ የኔፍሊም ዝርያዎች ዓለም ሴራ እግዚአብሔር ሲያጋልጥ ሁላችንም እንረዳለን፡፡ እስከዚያ ድረስ የፈለገው ሆ ይበል፣ የፈለገው እግዚአብሔርን ያዳምጥ፡፡ ሠይጣን ነገሮችን ክፋት በሆኑ ብቻ የሚሰራ ከመሰለን እንወድቃልን፤ ጥበበኛ ስለሆነ ለመጣል ካሰበ መልካም እያስመሰለም የራሱ ያደርጋልና፡፡ ኢትዮጵያ ላይ ዘረኝነትን የዘራ ማን ሆነና? እኔ የሚመኘው እና የሚሰራው ቅድስት ቤተክርስቲያን የክርስቲያኖች ሁሉ መሰብሰቢያ እንጂ የአማራ፣ የኦሮሞ፣ የትግሬ፣ የወለይታ… ወዘተ ብቻ መሰብሰቢያ እንዲትሆን አይደለም፡፡አሁን እየሆነ ያለውስ የአንድ ቋንቋ -አማርኛ ተናጋሪ አማኞችን መሰብሰብ አይደል እንዴ ያለው? አይደለም ካላችሁ በተለይ ማኅበረ ቅዱሳን ጅማ ማእከል ውስጥ ያላችሁ/የነበራችሁ ስንጨቃጨቅበት የነበረው ጉዳይ እኔም የተጠላሁበት የምንተዋወቅ ሰዎች አላችሁ፡፡ በቀጣዩ ጽሑፌ ይቀጥላል፡፡ በስመ ማኅበረ ቅዱሳን ዘረኝነትህን ማስፋፋት አትችልም፡፡